|
የመራጮች ምዝገባ ቀን ከመጠናቀቁ በፊት በቡራዩ ከተማ ከተጠበቀው ህዝብ በላይ በመራጭነት ተመዘገበ |
|
|
|
|
ጥር 30 ቀን 2002
በቡራዪ ከተማ አስተዳደር ከተጠበቀው በላይ ሕዝብ ለመራጭነት ለመመዝገብ በመምጣቱ በምርጫ ሕጉ መሰረት አዳዲስ መዝገቦች ተከፍተው ምዝገባ እየተካሔደ መሆኑን የከተማዋ ምርጫ ጽሕፈት ቤት አስታወቀ፡፡ ጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ባይሳ ረጋሳ እንዳስታወቁት በከተማዋ በመራጭነት ይመዘገባል ተብሎ የተጠበቀው 31ሺህ 67 ህዝብ የመራጮች ምዝገባ ቀን ከመጠናቀቁ ከ13 ቀን በፊት መመዝገብ ችሏል፡፡
እስከ ጥር 27 ድረስ ከተመዘገበው ህዝብ በተጨማሪ በመራጭነት ለመመዝገብ ወደ ምርጫ ጣቢያዎች ከጥር 28 ጀምሮ መምጣት የጀመረው ህዝብ ለማስተናገድ በምርጫ ሕጉ መሰረት አዳዲስ መዝገቦች ተከፍተው የምርጫ ምዝገባው እንዲቀጥል እየተደረገ መሆኑንንም አስታውቀዋል፡፡
የምርጫ ጽሕፈት ቤቶች የተመደበላቸውን የ1ሺሀ ሰው መመዝገቢያ መዝገብ የሕዝብ ታዛቢዎች በተገኙበት በመዝጋትና ከክልል ምርጫ ጽሕፈት ቤት ጋር በመወያየት በአዲስ መልክ ስራቸውን መቀጠላቸውንም አስረድተዋል፡፡ በዘንድሮ ምርጫ ህዝቡ በስፋት የምርጫ ጊዜው ከመጠናቀቁ 13 ቀናት በፊት በስፋት ወደ ምርጫ ጣቢያዎች ቀርቦ በመመዝገብ ያሳየው ይሀው ከፍተኛ ተሳትፎ እስከ አሁን ከተደረጉት ምርጫዎች የተለየ እንደሚያደርገውም ገልፀዋል፡፡
በከተማዋ አዲስ መዝገብ ተከፍቶ ምዝገባ ማከናወን በመጀመሩም ለምርጫ የተመዘገበው ህዝብ በየቀኑ በ100 ያህል እየጨመረ መምጣቱን አስረድተዋል፡፡ በከተማዋ ከእቅድ በላይ ተመዝጋቢ ሊመጣ የቻለው ሕብረተሰቡ አስተሳሰብ በማደጉና በአገሪቱ ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ ዲሞክራሲያዊ ባሕል እየተጎለበተ በመምጣቱ ነው ብለዋል፡፡ የቦርዱ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ መሐመድ አብድራሕማን በበኩላቸው በየትኛውም የምርጫ ጣቢያ ከአንድ ሺህ በላይ ተመዝጋቢ ሊመጣ ቢችል ከክልሉ ምርጫ ጽሕፈት ቤት ጋር በመነጋገር በአዲስ መዝገብ የመራጮች ምዝገባ ለመጀመር የሚያስችል አሰራር ይፈቀዳል ብለዋል፡፡ |